Monday, October 8, 2012

ኦህዴድ ጁነዲን ሳዶን አሰናበተ


በኢህአዴግ ድርጅቶች ውስጥ ከፍተኛ መተራመስ ውስጥ የሚገኙት የህወሃት እና የኦህዴድ ድርጅቶች መሆናቸውን በተደጋጋሚ ባቀረብናቸው ዘገባዎች መግለጻችን ይታወሳል። ህወሃት ከመለስ ዜናዊ ሞት በኋላ፤ አባይ ወልዱን በሊቀመንበርነት መርጦ ስራውን ቀጥሏል። የኦሮሚያው ኦህዴድ ደግሞ፤ አዲስ ጠቅላይ ሚንስትር ከተሾመ ወዲህ በኩርፊያ እና በቁጭት እየተተራመሰ ይገኛል። የኦህዴድ ሊቀመንበር አቶ አለማየሁ ታሞ አልጋ ላይ ከዋለ የሰነበተ ሲሆን፤ በሱ ምትክ አዲስ ሊቀመንበር የመምረጡ ሂደት በራሱ ሌላ ውዝግብ አስነስቷል። ይህ በእንዲህ እንዳለ የኦህዴድ አባላት ሰሞኑን ባደረጉት ስብሰባ ጁናዲን ሳዶን ከስራ አስፈጻሚነት አሰናብተዋል። የሪፖርተር ጋዜጣ ሙሉ ዘገባ ቀጥሎ ቀርቧል።
የኦሕዴድ ሥራ አስፈጻሚ ከመስከረም 21 ቀን እስከ መስከረም 24 ቀን 2005 ዓ.ም. ባካሄደው ዓመታዊ ጉባዔው ላይ፣ በሟች እናታቸው መኖሪያ ላይ እያሠሩት ካለው መስጅድ ጋር በተያያዘ የተገመገሙት ሚኒስትር ጁነዲን፣ ከፍተኛ የዲሲፕሊን ጉድለት መፈጸማቸውንና ካሉበት ኃላፊነትና ሥልጣን አኳያ ተገቢ ያልሆነ ሥራ መሥራታቸው በዋናነት እንደተገመገሙበት ምንጮቹ አረጋግጠዋል፡፡
አቶ ጁነዲን በእናታቸው የኑዛዜ ቃል መሠረት በመኖሪያ ቤታቸው ላይ መስጅድ ለማስገንባት፣ በሚኒስትርነታቸው ሳይሆን በግለሰብ ደረጃ ለመስጅዱ ማስጨረሻ ከሳዑዲ ዓረቢያ ኤምባሲ ዕርዳታ በመጠየቃቸው፣ የመስጅዱ የመጀመሪያ ደረጃ ምርቃት ሲደረግ በኢትዮጵያ የሳዑዲ ዓረቢያ አምባሳደር ተገኝተው 500 ቅዱስ ቁርአንና 50 ሺሕ ብር ዕርዳታ መስጠታቸውን ራሳቸው አቶ ጁነዲን በጻፉት ደብዳቤ አረጋግጠዋል፡፡
ባለቤታቸው አምባሳደሩ የሰጡትን 50 ሺሕ ብር ለመቀበል ኤምባሲ ሄደው ተቀብለው ሲወጡ፣ ለሽብር ተግባር የሚውል ገንዘብ ተቀብለዋል በሚል ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥር መዋላቸው መዘገቡ ይታወሳል፡፡ አቶ ጁነዲን በጻፉት ደብዳቤ ግን ባለቤታቸው የተከበሩ የቤት እመቤት መሆናቸውን ገልጸው ነበር፡፡
በዚህም ምክንያት በኦሕዴድ ሥራ አስፈጻሚ ስበሰባ ላይ በተደረገው ግምገማ፣ ከሥራ አስፈጻሚነት ተነስተው በተራ አባልነት እንዲቀጥሉ መወሰኑን ምንጮቹ አረጋግጠዋል፡፡
ድርጅቱ የ2004 ዓ.ም. በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸምን አንድ በአንድ የገመገመ መሆኑን የገለጹት ምንጮች፣ በፀጥታው ዘርፍ በተለይ ቦረና አካባቢ ተፈጥሮ በነበረው ግጭት ላይ ድክመት መታየቱንና ወደፊት ሊታሰብበት እንደሚገባ ሰፊ ውይይት እንደተደረገበት ተናግረዋል፡፡
በሪፖርቱ ላይ የታዩትንና ድክመት ያለባቸውን አንዳንድ የሥራ ዘርፎች በቀጣይ እንዲስተካከሉ ሐሳብ ተሰጥቶ ጉባዔው መጠናቀቁ ታወቋል፡፡ በድርጅቱ ውስጥ ያሉ አመራሮች እንዳሉ እንዲቀጥሉ ከማድረግ ውጭ ከኃላፊነቱ የተነሳም ሆነ የተሾመ አመራር እንደሌለ ታውቋል፡፡
ምንጭ፡ ሪፖርተር ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment